ሰሞነ ህማማት ማለት ምን ማለት ነው

 
 
 
 
 
ሰሞነ ህማማት ማለት ምን ማለት ነው 
ሰመነ - ማለት (ሳምንት) ሳምንት አደረገ ማለት ነው ፡፡ይሔውም ከእለተ ሆሳዕና ሰርክ እስከ ትንሳኤ ሌሊት ያለውን ጊዜ እና ቀናት የሚያመለክት ነው ፡፡

ሀመ - ማለት ታመመ ማለት ሲሆን ይህም የሰውን ዘር ሁሉ ከዳቢሎስ ባርነት ነፃ ለማውጣት ጌታችን አምላካችን መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፈቃዱ የተቀበላቸውን ፅዋተ መከራዎች የሚያሳስብ ነው ፡፡

የሰሞነ ህማማት እለታት ያመተ ኩነኔ ወይም የአመተ ፍዳ ምሳሌዎች ናቸው ፡፡ክርስቲያኖች የክርስቶስን ውለታ እያሰቡ እጅግ የሚያዝኑበት የሚያለቅሱበት የሚሰግዱበት ቤት ንብረታቸውን ትተው ከሌላው ቀናትና ጊዚያት በተለየ መልኩ ቤተ አምላካቸውን የሚማፀኑበት ጥዋት ማታ አምላካቸውን ደጅ የሚጠኑበት ሀጢያታቸውን በቤተክርስቲያን አደባባይ ለካህኑ የሚናዘዙበት በአመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ሳምንት ነው ፡፡

በዚህም ሳምንት ውስጥ ብዙ አዝማደ መባልዕት ወይም ብዙ ምግብ አይበላም ፡፡ ይልቁንስ በመራብ በመጠማት በመስገድ በመፀለይ በመፆም በየ ሰአቱ የጌታችን የአምላካችንን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራውን ህማሙን ግርፋቱን ድካሙን በማሰብ ይዋላል ፡፡
ከቅዱሳን መፃህፋት የጌታን ያምላካችንን መከራውንና ድካሙን የሚያስታውሱ ከትንቢተ ኢሳያስ ,ከትንቢተ ኤርሚያስ ,ከመዝሙረ ዳውይት ግብረ ህማማት በየሰአቱ ይነበባል፡፡

መስቀል መሳለም የለም ካህናትም እግዚአብሔር ይፍታህ አይሉም ፡፡ የሳምንቱ ስርአተ ፍትሀት አይደረግም ፡፡ ይኸውም ይህ ሳምንት ከሞት ወደ ሒወት የሸጋገርንበት ከጨለማ ወደ ብርሀን የተጓዝንበት የመሸጋገሪያ ወራት ምሳሌ በመሆኑ ነው ፡፡

በእለተ ምፅአት መላእክት የመለከትን ድምፅ እንደሚያሰሙ የዳግም ምፅአትን እለት በማሰብ ምዕመናን ጥሪውን ሰምተው ከዚያም አስቀድመው የበአሉ ታዳሚዋች መሆናቸውን ለማጠየቅ በዚህ ሳምንት ዳቆኑ ቃጭሉን እያቃጨለ ምዕመናኑን ያሳስባል ፡፡

ለመላው የኦርቶዶክስ ሀይማኖት ተከታዮች ይህ ሰሞነ ህማማት ከአምላካችን ጋር የምንገናኝበት የንስሀ የፅም የፀሎት ጊዜ ይሁንላችሁ ይሁንልን አሜን አሜን አሜን !!! ወስብሐት ለእግዚአብሔር
 
Suorce: